Thursday, February 12, 2015

ለምን እናንብብ?


የምናነበው መጀመሪያ ለራሳችን ነው። ለራሳችን አንብበን ነው ቀጥሎ ለሌሎች የምንተርፈው። በአስራ ሰባት ዓመቴ ወደ መርከበኞች ትምህርት ቤት ገብቼ ነበር። ከተማርኳቸው የማይዘነጉ የእሳት ማጥፋት መመሪያዎች አንዱመጀመሪያ ራስህን ለማዳን በአግባቡ ልበስ፤ ከዚያ በኋላ ሌሎችን ከእሳቱ ለማውጣት ተንቀሳቀስይላል። ነገርየው መንፈሳዊ አንድምታ እንዳለው የተረዳሁት ዘግይቼ ነው። አሁንም በምበርበት አውሮፕላን ሁሉየአየር እጥረት ከተፈጠረ ከጣሪያው የሚወርደውን ጭንብል ያጥልቁ፤ ከዚያ በኋላ ሌሎችን መርዳት ይችላሉሲባል እሰማለሁ።

በእኔ አተያይ ይህ መርኅ ጥርት ብሎ የገባው ሰው ቢኖር ጳውሎስ ነው። ለመንፈሳዊ ልጁ ጢሞቴዎስ እንዲህ ብሎታልና።ስትመጣ በጢሮአዳ ከአክርጳ ዘንድ የተውሁትን በርኖሱንና መጻሕፍቱን ይልቁንም በብራና የተጻፉትን አምጣልኝ” 2 ጢሞ 413 ይኸው አንባቢ ሰባኪ ነው ከመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ብዙዎቹን የጻፈ።

ሁለተኛው ታሪክን ለመቀየር ነው። ልጆቼ በሚማሩበት ትምህርት ቤት አንድ ነገር አስረግጠው ነግረዋቸዋል።አንባቢዎች መሪዎች ናቸው (ሪደርስ አር ሊደርስ) ብለው። አሁን ልጆቼና ንባብን ማለያየት የኔ ትልቁ ፈተና ሆኗል። መጽሐፍ ይዘው ከተቀመጡ ለምግብ እንኳ የምጠራቸው አንድም በልመና አልያም በቁጣ ነው። አሜሪካውያኑ የገባቸው አንድ እውነት ያለ ንባብ መጪውን ጊዜ መቀየር አይቻልም የሚል ሳይሆን አይቀርም ። በምርኮ ምድር የተደላደለውን ሕዝብ በቃህ ብሎ ወደገዛ መሬቱ የመለሰው ዳንኤል የዘመኑን ፍጻሜ ያስተዋለው የኤርምያስን መጽ በማንበብ ነበር (ዳን. 9:2) በርግጥም ከጸሎት ቀጥሎ ለሰዎች የምንርፍበት ትልቅ እሤት ንባብ ነው።

በመጨረሻም ከምንም ይልቅ ማንበባችን ጥበብን ፍለጋ ነው። እንደምናውቀው ጥበብ የምትገኘው በንባብ ብቻ አይደለም። በቅድሚያ ከባለቤቱ በመለመን ትገኛለች። ቃሉከእናንተ ግን ማንም ጥበብ ቢጎድለው፥ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፥ ለእርሱም ይሰጠዋልይላልና (ያዕ. 1:5)

ቀጥሎም በፈሪሃ እግዚአብሔር ትጨበጣለች። ይህንን የምሳሌ መጽሓፍየጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ ሰነፎች ግን ጥበብንና ተግሣጽን ይንቃሉበማለት ያበራልናል (ምሳ.1:7) ፈቀቅ ስንልም ለትኁታን ጥበብ  እንደምትሰጥ ያው መጽሐፍ እንዲህ ይነግረናል።ትዕቢት ስትመጣ ውርደትም ትከተላለች፤ በትሑት ዘንድ ግን ጥበብ ትገኛለች (ምሳሌ 11:2)

 ሌላውና ንባብ ነው። ንባብ ስንል ደግሞ በተለይም መጽሐፍ ቅዱስን መመርመር ላይ ያተኩራል። እናም ጥበብን የራስ ለማድረግ ሌላው ዘዴ ቃሉን ማጥናት ነው። ለምን ቢሉ ቃሉን ማሰላሰል ከፍተኛ ጥበብን ከማስገኘቱም በላይ ሥራዬ ብሎ ቃሉን በማጥናት የሚሸመተው ጥበብ አስተማማኝ ነው።

No comments:

Post a Comment