Saturday, March 31, 2012

እዚሁ እንገናኝ!

ጊዜ ባገኝ፤
የማደርገውን አውቃለሁኝ፤
የመጻሕፍቴ ገጾች ወደቅን እስኪሉኝ፤
አነባቸው ነበር እየደጋገምኩኝ።
ጊዜ ባገኝ
እጽፍ ነበር በርካታ ደብዳቤዎች፤ 
ያልመለስኳቸውን ለብዙ ሳምንቶች፤
ለብዙ ብዙ ሰዎች።
ጊዜ ባገኝ
እከፍል ነበር የስልኬን ወረት፤
ያጠራቀምኩትን ለሳምንታት፤
ደግሜም አልዘገይ በውነት።
ጊዜ ባገኝ
ሕይወቴን እቃኛለሁ በዚያ፤
ጊዜ ይኖረኝ ዘንድ መግባቢያ፤
ከሚስቴ ጋር መቀራረቢያ።
ጊዜ ባገኝ
ግሩም የደስታ ሕልም፤
ከወር ከዓመት ከአስር ዓመት በኋላ ወይም፤
ግን ይህን መጨረስ አልችልም፤
 ምክንያቱም ጊዜ የለኝም። 

ገጣሚው ቶማስ ኤል ሜሰን እንዳለው እኔም ጊዜ ሳገኝ እያልኩ ያዘገየሁት አንድ አሳብ ነበረኝ። ይኸውም አንድ የጽሑፍ ሠሌዳ( Blog) ከፍቼ አንዳንድ አሳቦችን ከናንተ ጋር መካፈል ነው። ዛሬ ሞላልኝ። ዳር ላይ ቆሜ ሳመነታ “ትችላለህ” ብላ ወደዚሁ የገፋችኝን ብሌንን ላመሰግን ይገባኛል። ይህንኑ የጽሑፍ ሠሌዳ “ከአለፍ አገደም” ብዬ ሰይሜዋለሁ። ምክንያቱ አሁንም  የጊዜ ጉዳይ ብቻ መሆኑ ይሰመርበት። ከተማሪነቴ ከሙሉ ጊዜ ሥራዬ አልፎ አልፎ ከምሠራው የማስተርጎም ሥራ ቤተሰብ ከማስተዳደሩና መጻሕፍትን ከማዘጋጀቱ ባሻገር መሆኑ ነው። ስለሆነም ከአለፍ አገደም እዚሁ እንገናኝ! በአጋጣሚ በዚህ ያላካተትኳቸውና ቢያነቡ አይጠሉም የምትሏቸው ቢኖሩ መልዕክቱን አድርሱላቸው ስል በትሕትና እጠይቃችኋለሁ።
ወዳጃችሁ
ዓለማየሁ ማሞ


http://alemayehuwrites.blogspot.com/

Tuesday, March 27, 2012

ስብሐት ገብረእግዚአብሔርን በትውስታ


ከጋሼ ስብሐት ጋር በትልቅ ርቀት እንተዋወቅ ነበር። ትውውቁን የፈጠረው ቢያንስ ለሦስት ዓመታት በዕለታዊ ጋዜጣ ላይ አብረን መሥራታችን ነው። ርቀቱን ያስከተለው ደግሞ ልዩነታችን ነበር። እርሱ ትልቅ እኔ ትንሽ፤እርሱ አገር የሚያውቀው ጥበብ አሳማሪ እኔ ደግሞ የመስሪያ ቤታችን ፈታሾች እንኳ ደባብሰው የሚያስገቡኝ ጀማሪ እርሱ በጎልማሳነት ዕድሜ ያለ ሰው እኔ ቢያንስ በሦስት አስር ዓመታት የማንሰው እርሱ በመስኩ የተማረ እኔ ወደኮሌጅ ፊቴ ያልዞረ.. ወ.ዘ.ተ ስለነበርን ብቻ ነው። በነዚያ ሦስት ዓመታት ግን ስለእርሱ ሦስት የሚያክሉ ገጠመኞች አሉኝ። ለዛሬ የማነሳው መቼውንም የማልረሣው ገጠመኝ ግን ይሄ ነው። አንድ ማለዳ ወደቢሮዬ ...ይመጣል። ሰላምታ ከተለዋወጥን በኋላ

“ ዓለማየሁ ነው እሚሉህ አይደል?” ይለኛል።

“ ዓለማየሁ ማሞ” አልኩት ሁለት ስለነበርን

“ አንድ ጥያቄ አለኝ?”

“ ምን?” አልኩ በብዙ ጥርጣሬ

“ መጽሐፍ ቅዱስ ታነባለህ አሉ”

“ልክ ነው፡ ጥያቄህ ስለርሱ ነው?”

“ኢየሱስ ነጋዴዎችን በጅራፍ ያባረረው የትኛው ቦታ ላይ ነው?”

“እዚህ ጋ” አልኩት በስተኋላ ከእበላ ባዮች ብዙ ስደት ያመጣችብኝን መጽሐፍ ከመሳቢያዬ ውስጥ አውጥቼ።

ከአንገቱ ዝቅ ብሎ አመስግኖኝ ወጣ። ከመካከላችን ትልቁ ሰውዬ ያሳየኝ ትኅትና መቼውንም የምዘነጋው አይደለም። በበነጋው እግረ መንገድ ላይ ያችን ጥቅስ ተጠቅሞና ኢየሱስን ከቼጉቬራ ጋር አነጻጽሮ አስቂኝ ጽሑፍ አሰፈረ። እያመመኝ አነበብኩት። ምክንያቱም ኢየሱስ በዚያን ዘመን ለእኔ ከታላላቅ የሃይማኖት መሪዎች አንዱ ብቻ ሳይሆን ብቸኛ አዳኝም ነበር። አሁንም ነው! ግን ሳገኘው ያስለመድኩትን የአክብሮት ሰላምታ አላጓደልኩም። ለምን ቢሉ አንድም ያመነበትን የመጻፍ መብቱን አክብሬ አልያም ባየሁበት ትኅትና ተሰብሬ።

ርቀታችን ብዙ ሰፍቶ ብዙም ሳይቆይ ፕሬስን ስለቅ የግንኙነታችን ርቀት ጨመረ። በ2001( እ.አ.አ) ወደአሜሪካ ስመጣ ደግሞ ላንተያይ ተለያየን። ከ10 ወራት በፊት በአዲስ አበባ ቆይታዬ የአፍሪካ ደራሲያንን ዓለም አቀፍ ጉባኤ ተካፍዬ ነበር። በዚያ የጋሼ ስብሃትን ማስታወሻ ያሳተመውን ዘነበ ወላን ጨምሮ በርካታ የሥነ ጽሑፍ ሰዎችን እንጂ አርሱን አላየሁትም። ባየው እወድ ነበር። አልሆነም። ርቀቱ በዚህ ምድር ብቻ ሳይሆን በሁለት ዓለማት መካከል ሆኖአልና
!